languageIcon
search
search
brightness_1 ከመተኛት በፊት እሳትን ማጥፋት

ከዚህ በላይ በሰፈረው የጃቢር -የአላህ መልካም ሥራዎቻቸውን ይውደድላቸው- ሐዲሥ ነቢዩ -የአላህ እዝነትና ሰላምታ በእሳቸው ላይ ይሁን-፣ “ስትተኙ መብራቶችን አጥፉ፡፡” ብለዋል፡፡

ኢብን ዑመር -አላህ መልካም ሥራዎቻቸውን ይውደድላቸው- እንዳስተላለፉት ነቢዩ -የአላህ እዝነትና ሰላምታ በእሳቸው ላይ ይሁን፣ “በምትተኙበት ወቅት እሳትን በቤታችሁ ውስጥ አትተዉ፡፡” ብለዋል፡፡ ሐዲሡን ሙሰሊም በሐዲሥ ዘገባ ቁጥር (2015) ላይ ዘግበውታል፡፡

ስለዚህ እዚህ ላይ እንዲያበራ ክር ያለበት ኩራዝ ወይም ማሾ ለአብነት ተጠቀሰ እንጂ ከዚህ ጋር በማዛመድ ማንኛውም ለቃጠሎ ምክንያት የሚሆንን ነገር በዚህ ሥር በማካተት መጥፋት ይኖርበታል፡፡ ምክንያቱም ነቢዩ -የአላህ እዝነትና ሰላምታ በእሳቸው ላይ ይሁን- እንደነገሩን እሳት በርግጥ ለኛ ጠላት ነው፡፡

በዚህ መሰረትም፡- አንድ ሰው እሳቱ ምንም እንደማይለው ደህንነት የሚሰማው ከሆነና በዙሪያው እሱን የሚያባብስ ነገር የሌለ መሆኑን ካረጋገጠ በዚህ ጊዜ መተዉ ምንም ችግር የለውም፡፡ ድንጋጌውም በመኖሩና ባለመኖሩ ላይ ነው፡፡

 

brightness_1 የሚተኛበትን ፍራሽ ከመተኛቱ በፊት ማራገፍ

አቢ ሁረይራህ -አላህ መልካም ሥራዎቻቸውን ይውደድላቸው- እንዳስተላለፉት ነቢዩ -የአላህ እዝነትና ሰላምታ በእሳቸው ላይ ይሁን-፣ “አንዳንችሁ ወደመኝታው ካመራ በውሰጠኛው ሽርጡ ፍራሹን ያራግፍ፡፡ በእሱ ላይ ምን እንደተተወ አያውቅም፡፡ ከዚያም ቢስሚክልላሁምመ ወደዕቱ ጀንቢ ይበል... ይበል፡፡” ሐዲሡን ቡኻሪ በሐዲሥ ዘገባ ቁጥር (6320)፣ ሙስሊም ደግሞ በቁጥር (2714) ላይ ዘግበውታል፡፡

ከዚህ በላይ ከሠፈረው በውስጠኛ ሸርጡ ፍራሽን ማራገፍ ነቢያዊ ፈለግ እንደሆነ ግልጽ ይሆንልናል፡፡ በዚህም መሰረት ማራገፉ ሶሰት ጊዜ ሲሆን የአላህን ስም ማውሳትም ነቢያዊ ፈለግ ነው፡፡

በላጩ በውሰጠኛው ልብስ ማራገፉ ነው፡፡ ከዑለሞች መካከል በማንኛውም ነገር ማራገፍ ይቻላል ያሉ ሲኖሩ ዋናው ቁም ነገሩ የፍራሹ መራገፍ ነው፡፡ ይህን ካሉት ዑለሞች መካከል ኢብን ጀብረይን -አላህ ይዘንላቸው- ሲሆኑ እሳቸውም፣ ‹‹በውስጥ ሽርጥ ማራገፍ መስፈርት አይደለም፡፡ ፍራሹን ሁሉ የሚያራግፈው ቢሆንም ወይም በጥምጣም ወይም ወ.ዘ.ተ በመሳሰሉት ቢያራግፈው የታሰበው ተፈጻሚ ሆኗል፡፡›› ብለዋል፡፡ የእሳቸውን ፈታዋ በቁጥር (2693) ይመልከቱ፡፡

brightness_1 ሌሊት ላይ ከእንቅልፉ የነቃ ሰው ይህን ዚክር ማለቱ ነቢያዊ ፈለግ ነው፡-

ከዑባደህ ኢብን አስ-ሳሚት -አላህ መልካም ሥራዎቻቸውን ይውደድላቸው- እንዳስተላለፉት ነቢዩ -የአላህ እዝነትና ሰላምታ በእሳቸው ላይ ይሁን-፣ “ሌሊት ላይ ድንገት የነቃና  ላ ኢለሀ አልለልላህ ወሕደሁ ላ ሸሪከ-ልላህ ለሁ-ልሙልኩ ወለሁ-ልሐምዱ ወሁወ ዐላ ኩልሊ ሸይኢን ቀዲይር አልሐምዱሊልላህ የሱብሓነ-ልላህ ወላ ኢላሀ ኢልለልላህ ውልላሁ አክበር ወላ ሐውለ ወላ ቁውወተ ኢልላ ቢልላህ፡፡ /ከአላህ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ ብቻውን ነው፡፡ አጋር የለውም፡፡ ንግሥና ለሱ ነው፡፡ ምስጋናም ለእሱ ነው፡፡ እርሱ በሁለም ነገር ላይ ቻይ ነው፡፡ ምስጋና ለአላህ ይሁን፡፡ ከከንቱና ውድቅ ንግግሮች አላህ በእጅጉ ጠራ፡፡ ከአላህ በስተቀር ሌላ አምላክ የለምም፡፡ አላህ ታላቅ  ነውም፡፡ ብልሐትም ሆነ ሃይል በአላህ ካልሆነ በስተቀር በሌላ የለም፡፡/  ያለና ከዚያም አልላሁምመ ኢግፊር ሊ፡፡ /አላህ ሆይ! ወንጀሌን ማርልኝ፡፡/ ወይም ዱዓእ ካደረገ ዱዓው ምላሽ ያገኛል፡፡ ዉዱእ አድርጎ ከሰገደ ሰላቱ ተቀባይነትን ያገኛል፡፡” ሐዲሡን ቡኻሪ በሐዲሥ ዘገባ ቁጥር (1154) ላይ ዘግበውታል፡፡

ኢብን አሢር -አላህ ይዘንላቸው-፣ ‹‹“ሌሊት ላይ ድንገት የነቃ” ማለት ከእንቅልፉ የባነነ ማለት ነው፡፡››  ብለዋል፡፡ ኢብን አሢር፡- አን-ኒሃያ ፊ    ገሪቢ-ልአሠር  ገጽ ፡ 108፡፡

በዚህ ሐዲሥ ውስጥ ሁለት የላቁ የሆኑ ብስራቶች አሉ፡፡ እነርሱም፡- ከእንቅልፉ ድንገት ነቅቶ፣ “ላ ኢለሀ አልለልላህ ወሕደሁ ላ ሸሪከ-ልላህ ለሁ-ልሙልኩ ወለሁ-ልሐምዱ ወሁወ ዐላ ኩልሊ ሸይኢን ቀዲይር አልሐምዱሊልላህ የሱብሓነ-ልላህ ወላ ኢላሀ ኢልለልላህ ውልላሁ አክበር ወላ ሐውለ ወላ ቁውወተ ኢልላ ቢልላህ፡፡ /ከአላህ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም፡፡ ብቻውን ነው፡፡ አጋር የለውም፡፡ ንግሥና ለሱ ነው፡፡ ምስጋናም ለእሱ ነው፡፡ እርሱ በሁለም ነገር ላይ ቻይ ነው፡፡ ምስጋና ለአላህ ይሁን፡፡ ከከንቱና ውድቅ ንግግሮች አላህ በእጅጉ ጠራ፡፡ ከአላህ በስተቀር ሌላ አምላክ የለምም፡፡ አላህ ታላቅ  ነውም፡፡ ብልሐትም ሆነ ሃይል በአላህ ካልሆነ በስተቀር በሌላ የለም፡፡/” የሚለውን ዚክር ያለ ሰው ሁለት ብስራቶች አሉት፡፡  

አንደኛው፡- “አልላሁምመ ኢግፊር ሊ /አላህ ሆይ! ወንጀሌን ማርልኝ፡፡/ ወይም ዱዓእ ካደረገ ዱዓው ምላሽ ያገኛል፡፡”

ሁለተኛ፡- ተነስቶ ዉዱእ አድርጎ ከሰገደ ሰላቱ ተቀባይነት አለው፡፡ እነዚህን ችሮታዎች ላጣቀመን አላህ ምስጋና ይገባው፡፡ ለተግባሩ አጋጣሚውን እንጠይቀዋለን፡፡